የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ይናገር ደሴ (ዶ/ር) ከዛሬ ጥቅምት 7 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ከ100 ሺሕ ብር በላይ እጃቸው ላይ የሚገኝ ግለሰቦች ገንዘብ ተወርሶ ለመንግሥት ገቢ እንደሚሆን አስታውቀዋል፡፡
የገንዘብ ቅያሪውን አስመልክተው ትናንትና፣ ጥቅምት 6 ቀን 2013 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ ከጥቅምት 7 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ገንዘብ መቀየር የሚቻለው ከ100 ሺሕ ብር በታች ብቻ መሆኑን የገለጹት የብሔራዊ ባንክ ገዥው፣ “ከ100 ሺሕ እስከ 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በአዲሱ የገንዘብ ኖት ለመቀየር የተቀመጠው ቀነ ገደብ ዛሬ አርብ፣ ጥቅምት 6 ቀን 2013 ዓ.ም. አብቅቷል” ብለዋል፡፡ እስከ 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ለመቀየር የተያዘው የጊዜ ገደብ እንደማይራዘምም ጨምረው ገልጸዋል። ይህን ተከትሎ ከነገ ጀምሮ እጃቸው ላይ ከ100 ሺሕ ብር በላይ የያዙ ግለሰቦች ገንዘባቸው ተወርሶ ለመንግሥት ገቢ እንደሚሆን አስታውቀዋል፡፡
ከ100 ሺሕ ብር በታች የቀድሞውን የገንዘብ ኖት ይዘው የሚመጡ ሰዎች ግን ከነገ ጀምሮ እንደሚስተናገዱ በሰጡት መግለጫ ያስታወቁት ይናገር ደሴ (ዶ/ር)፤ ከ100 ሺሕ ብር በታች የገንዘብ ቅያሪው ለሁለት ወራት እንደሚቀጥልና አፈጻጸሙ እየታየ የጊዜ ገደቡ ሊያጥር እንደሚችል ገልጸዋል፡፡ ባንኩ በቀሩት ጊዜያት በአርሶ አደርና አርብቶ አደሩ እጅ የሚገኘውን ገንዘብ የመቀየር ሥራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ጨምረው ተናግረዋል፡፡
Leave a Reply